Tuesday 29 August 2017

መልካም አገዳደል ወይስ መልካም አስተዳደር?


(በ መሳይ እስከዳር አበራ)

     ባልጠበኩት በተረገመ ባልተጠራ አንድ ቀን ለምድር የከበደ ዝናብ ጣለ የደሀ ጎጆዬን ጎርፍ አባ ሳሙኤል ግድብ ጠቅልሎ ሳይከታት ለማትረፍ የጣራዬን ቀዳዳ ለመድፈን ብጥር ይባስ እየከፈትኩለት ቤቴን ደጅ አድርጌው ቁጭ አልኩ! ጠብ ሲል ስደፍን ጠብ ሲል ስደፍን እንዲሁ ሌሊቱን አደርኩ

     የቤቴን ክዳን ቆርቆሮ ላስተካክል ሳስብ ገና ለ ገና ከየት መጣ ያልተባለ መጥሪያ እጄ ላይ ደረሰ!… …ገና ለገና ዛሬ ጣሪያው አፈሰሰና ነገ ጣራ ሊቀይር ይችላል ተብሎ የጠቆመው ማን ይሆን?? እያልኩ ሳሰላስል… ………መቼም ሰው ሳይሆን ባለ አውሊያ ጠንቆይ መሆን አለበት ይህን መረጃ ለወረዳው ያቀበለው……በቃ የኛ ሰፈር ጠንቋይ ሳይቀር ተጠሪነቱ ለቀበሌ ሆኖ ይቅር ዘንድሮ ምን ተሻለን?  ……… ጠንቋዩም… ለሰይጣን ትቶ ለመንግስት አደረ  ማለት ነው? !……… እረ ደግ አደረገ እያልኩ ከማያውቁት መላአክ የሚያውቁት ሰይጣን ይሻላል ብዬ …በዚህ ስገረም ዋልኩ!……አሁን ነገ በለሊት ተነስቼ ጣራውን መቀየር አለብኝ ብዬ የተማከርኩት ከራሴ ጋር ነበር ለነዚህ ጠንቋዬች ስራ ደርቦ መስራት ምን ፋይዳ ይኖረው ይሆን? እየገረሙኝ  አይ መጨካከን ብዬ ወደ ተጠራሁበት ቢሮ አቀናሁ!

     ኧረ የሰው ጆሮ ግን በጣም ተሻሽሉዋል ጆሮው ከአፍ ሳይሆን ከልብ መስማት እና ማዳመጥ ጀምሯል ይሄ የአምስት አመቱ የትራንስፎርሜሽን እቅድ ውስጥ ይካተት አይካተት የማውቀው ነገር የለም! ግን እውነት እውነት እልሀለው ከራሴ በቀር ይሄን ቆርቆሮ ስለማስተካከል ያወራሁት አንድም ሰው አልነበረም አዕምሮየ እንኳን ይሄን ሲያስብ ኪሴ ይሄን ደባ አያቅም ነበር! ደሞዜ ከምፅአት ቀን አንድ ቀን ቀደም ብሎ እስኪመስለኝ ድረስ እሩቅ ነበር! ደሞዝ ከተባለ የመንግስት ደሞዝ የወንድ ልጅ ፔሬድ ነው ስለተባለ ከደሞዝ አልቆጥረውም!

     ጠሩኝ አደል? በሰአቱ ተነስቼ ወደ ወረዳው አመራሁ!
ገና የቁርስ ሰአት ቢሆንም የደንብ ስራ ሂደት ሀላፊው እኔ ስደርስ ምሳ ወተዋል

     እናት ገና እኮ ነው ሰአቱን እይው እስቲ ሁለት ተኩል ነው ስላት?… አንድ ፀሀፊያቸው ትሁን አፀያፊያቸው ትሁን በውል ያልገባችኝ እንስት በአይንዋ ፊቴን ሞነጫጨረችው… አይ በቃ እንግዲያው ስኳር ይኖርባቸው ይሆናል ለዚህ ነው እየበሉ የሚርባቸው ብዬ ወጣሁ!………በመብላት እረገድ የሚደረገውን ጥረት ለአገልግሎት ጥራት ቢደረግ ምንኛ ደግ ነበር! ልል ፈልጌ የፀረ ሽብር ህጉን አስታውሼ አፌን ለጎምኩ!

     ደንብ ለማክበር ደንብ የማይከበርበት ሀገር ላይ መኖሬ የሚያሳዝነኝ አንድ ወቅት ላይ  ቀለም ስትቀባ መተህ ማስፈቀድ አለብህ ተብሎ የቤቱ ግርግዳ  ቀለም በደንብ ማስከበር የስራ ሂደት ሃላፊው አማካኝነት  የተፈቀፈቀበት ሰው ስለማውቅ ነው!

  አንዴ ደሞ   የቤቱ ቁልፍ ጠፍቶት ለመቀየር የፈለገው ግለሰብ ወረዳ ድረስ መተህ በራፖር አመልክተህ የቁልፉን ቀዳዳ እንደማታሰፋው ቃል በመግባት ፈርም የተባለ ግለሰብ ስለማውቅ ነው!

     ያሳያቹ…እኔ አድሳለው ያልኩት አፍርሼ አልነበረም አፍርሶ የመገንባት አቅሙም ጉልበቱም አልነበረኝም ሀሳቤ ይፈሳል ያልኩበትን ቦታ ወቶ መለጠፍ ነበር ብዙ ቦታ ስለምለጥፍ አዲስ የመጣ ቆርቆሮ መስሉዋቸው ቤቴን እንደ ጆፌ አሞራ ሊከብዋት ስለሚችሉ ነበር አስቀድሜ ጥሪዬን አክብሬ ቢሮ የተገኝሁት!

     ለማንኛውም ጠሪ አክባሪ ነው ብዬ ነበር የሄድኩት… እግሬን ወደ ቀበሌ ከማነሳ ሞቴን እመርጥ የነበርኩ ሰው እኮ ነኝ ዛሬ ግን የህግ መጥሪያ ሲደርሰኝ ምን ላድርግ ወደ ወረዳው አቀናሁ፡፡

     መቼ ነው? ስለኔ መጨነቅ የማትሰለቸው የሚለዉን ዘፈን እኔ መቼ ነው ስለኔ መጨነቅ ምትጀምረው? አያልኩ ገልብጬ በመዝፈን ያቀናሁት !…………በቃ እራት ብለው ሳይወጡ መክሰስ ላይ ወይ ምሳ ላይ  እመጣለው ብዬ አፀያፊዋን  ተሰናብቼ ወጣሁ።

     እኔ የሚገርመኝ የትም አይሄዱም  ለመስክ ስራ ይወጡና አስከ ሶስተኛ አንዱ ህገወጥ ግንባታ የገነባ ልማታዊ ሌባ ጋር ገብተው ጃንቦ አክትመው ይወጣሉ፡፡

      ሌላው በየ ህንፃ መሳሪያው መደብር ሰላይ ወይም ስኩፒኒ አስተኩኣሽ ያስቀምጣሉ ማን ቆርቆሮ ገዛ ማን ሚስማር አስላከ ተቀምጠው በአይነ ቁራኛ ይከታተላሉ አንተ ሀገር አማን ብለህ ኪሎ ኮፍያ ሚስማርህን ይዘህ ስትገባ በጎን እንደኔ መጥሪያ ይደርስሀል በቃ እንደትራፊክ እየተከታተሉ ኑሮህን እንዳታሻሽል ቤትህን እንዳታሳምር ቁም ስቅልህን በቅጣት እና የካብከውን በመናድ እንዲሁም በማፍረስ ፍዳህን ያሳዩሀል! አንድም ቀን ህገ ወጥ የተባለ ፎቅ ሲፈርስ አላጋጠመኝም ሁሌ የምስኪን ደሀ በዩኒሴፍ ድንኮን የተሰራ ጣራ ከንፋስ ተርፋ በደንቦች ስትገነጣጠል ማየት የሰርክ ተግባሬ ነው።

     ሌላው የሚገርመኝ የደንብ ስራ ሂደት ባለቤቱ ባለስልጣን ሳይሆን፣ የሊቀመንበሩ ነው ቢሮአቸው እላይ 5ተኛው ፎቅ ላይ ነው…ያው የሚገባው ይገባዋል ለምን እዛ እንደተሰቀሉ፡፡ እኛን አትደረሱብን ለማለት ነው፡፡ ልሰማችሁም ልረዳችሁም ላናግራችሁም ችግራችሁንም ልካፈል አንፈልግም ነው፡፡ ግልፅ አኮ ነው እሳቸው ከኛ ግብር እና ታክስ ተቆርጦ የሚከፈላቸውን ደሞዝ ብቻ ነው የሚፈልጉት !

     የትኛው አካል ጉዳተኛ ነው በዊልቸር ወቶ ችግሩን በአካል የሚያስረዳው? ያሳያቹ አሁን የዘጠና አመትዋ እማማ ናቸው ወይስ አባባ ናቸው በትኩሱ ጉልበታቸው እላይ ታች የሚሉለት ቀበሌ ጉዳይ ከማስፈፀም እኮ በፀሎት ከፈጣሪ ጋር ተነጋግሮ መግባባት ይቀላል… ይሄን አውቆ እዛ ተሰቅሎ ከሰው ከፍ ያለ ቦታ ላይ ሲቀመጥ ሰው ዝቅ አድርጎ ይገምታል! እኔ የኛ ሊቀመንበር ይገርሙኛል እንዳለፈበት አራዳ የዝቅተኛነት ስሜት ከተሰማህ ዛፍ ላይ ውጣ አይነት ፕሪንሲፕል ሲጠቀሙ እናደዳለሁ፡፡ ጊዜ ያወጣውን ጊዜ ያወርደዋል እና ጊዜ ያወጣውን እውቀት አስኪያወርደው አስከዛው ልብ ይሰጣቸው ብለን የደንብ የስራ ሂደት ባለቤት እስኪመጡ ልጠብቅ አስቤ ነበር! ነገር ግን የስራ ሂደት ሀላፊው እንደ ሙሽራ ደንበኛ ካላስጠበቁ ቢሮ ድርሽ አይሉም… መንግስታችን መልካም አስተዳደርን አረጋግጣለሁ ብሎ ሌት ተቀን ይቀደዳል እሳቸው መልካም ህዝብ በስልጣናቸው ከስክስ ይረጋግጣሉ!

     በተረገመ ሌላ ቀን ደሞ በከተማ ግብርና ለመደራጀት አንድ ለአምስት በሚባል ጥርነፋ እራሴን ላስር ተገኝቼ ነበር ………ልክስክስ እኮ ነኝ! አዲስ አበባ ላይ ሜካናይዝድ በሆነ የእርሻ መሳርያ ሰሊጥ ፣ ኑግ እና ለውዝ የምናመርት መስሎኝ ወደ ቀበሌ ከማምራቴ በፊት የተለያዩ ሀገራት ኤምባሲ ጋር በመሄድ ምርት ተቀባዬችን ከሊስታቸው ውስጥ አፈላልጌ ጨርሼ በስልክ ደውዬ ቀብድ ሁላ ሊሰጡኝ ተስማምተው የመንደር ውል ሁላ ተዋውዬ ጨርሼ ነበር …………… ዳሩ ምን ዋጋ አለው እጣ ሲጣል የደረሰን አሳ እርባታ ነበር… ይታያቹ አዲስ አበባ ላይ ታንኳ ቀዝፌ መረብ ዘርግቼ አሳ እያታለልኩ ሳጠምድ! ? ቀበናን ነው አቃቂን ልጠቀም ነው…
ያው እኔ ድሮም ታቃላቹ በጀርባዬ ብወድቅ እንኳን የሚሰበረው አፍንጫዬ ነው።

     በተረገመ ሌላ አንድ ቀን ደግሞ የቀበሌውን ብክነት ሊቀንሱ በሚችሉ ጉዳዬች ላይ ለመወያየት ተገኝቼ ነበር ስልጠናው የሶስት ቀን ቢሆንም በመጀመሪያው ግማሽ ቀን ላይ ሶስት ቀን ማባከን ምንድነው? በሚል ጉዳይ ላይ ለግማሽ ሰአት ተወያይተን ስልጠናው አልቆ የሶስት ቀን አበል ተከፍሎን ከአሰልጣኛችን ጋር ኪስ ሳንገባ የህዝብ ገንዘብ መንትፈን ብክለትን በፍሳሽ መልክ አስወግደን አልፈናል!

     እንግዲ መሬት የመንግስት ነው ይሉናል እኛ ስንማር መንግስት ማለት ህዝብ ነው ተብለናል! ታድያ ለመኖሪያ የሚሆን መሬት ስጡን ድርሻችን ስንል በሊዝ ግዛ ትባላለህ አንድ አባት ትርፍ የነበራቸውን መሬት ይዘው የቆዩ ቢሆንም ይሄን ያህል ብቻ ነው በካርታ የምንሰራሎት የተቀረውን በሊዝ ነው የሚገዙት ሲባሉ! …ሆ! ሊዝ ደሞ የምን ሀገር ገንዘብ ነው ብለው የጠየቁት አንዱ ማሳያ ነው!

     ሌላው ከዚህ ጋር ተያይዞ ትንሽ ጆሯቸው የሚሸውዳቸው አንድ አባት ነበሩ እና ሁሌ በሬዲዬና በቲቪ የእገሌ ቀበሌ ነዋሪዋች ለአባይ ግድብ የሚሆን "ቦንብ" ገዙ፤ የእገሌ ድርጅት ሰራተኞች ከወር ደሞዛቸውን ለአባይ ግድብ የአስር ሚሊዮን ብር "ቦንብ" ገዝተው አጋርነታቸውን ገለፁ የሚል ዜና በዝቶባቸው ነበር፡፡ ሰውየው ለልጃቸው አንድ ጥያቄ አነሱ ህዝቡ ግን ምን ሆኖ ነው ልጄ ለአባይ ለአባይ እያለ ቦንብ የሚገዛው ግብፅ ሳንሰማ ጦርነት ጀመረች እንዴ?… የታሪክ ባላንጣችን እስዋ ነች!… ልጅ ቀበል አደረገና አይደለም አባት ያው ቦንብነቱ ባይካድም ለማለት የፈለጉት ቦንድ ነው፡፡ ቦንድ ደሞ ምንድነው ልጄ?…… ሌላ ጥያቄ? አባ በባንክ የሚሰጥ የመተማመኛ ወረቀት ነው ቦንድ ማለት! …አሀ አባይን ፈርማቹ ለግብፅ ለመስጠት ነው ወረቀት ለአባይ የምትገዙት ግብፅ በባንክ መክፈሉዋ ነዋ ልጄ?…… እረ እንደዛ አደለም አባ! አባይን በህዝብ ገንዘብ መንግስት ገድቦ ለኛ መብራት ያለማቋረጥ እንዲደርሰን ማዋጣት ስላለብን ለተወሰነ ወቅት ወጪ የማይደረግ ገንዘብ ለባንኩ መስጠት ማለት ነው!…… አሀ መብራት እንዳይቋረጥ ነው እንዴ ደግ…መብራትማ ይቋረጥ እንጂ በታወቀ ሰአት ማጥፋት አስለምዶን ሙሉ ቀንማ መብራት  የለበትም… አሁን አህትህ እዛ የኤሌትሪክ አስቶቭ ላይ ሰርታ ከዛ ያጠፉታል አባዬ አታስብ ብላኝ ነው ምትሄደው… እንዲ ያለማቁዋረጥ ከለቀቁልንማ አሳስተው ከነ ድስታችን ያነዱናል… ይሄ መልካምም አገዳደል አደለም !

የኢትዬጵያ ህዝብ እኮ ጨለምተኛ ነው።
ምክንያቱም……
መብራት በአግባቡ አያገኝማ!

እንደ ኢትዬጵያ ደሞ መልካም አስተዳደር ፣ ዲሞክራሲ ፣ ነፃ ነት ፣ የቡድን እና የግለሰብ መብቶች ፣የመናገር፣ የመፃፍ እና ወዘተ መብቶች በእኩልነት የተረጋገጡባት ሀገር የትም የለ

በተገባር እኮ አደለም በከስክስ ነው የተረጋገጡት!

No comments:

Post a Comment

የፖለቲካ ባህላችን

አየሽ እዚህ አገር ከንቱ ፍረጃ አለ፤ አማኝ ሁሉ አክራሪ፤ ሙስሊሙ አሸባሪ፤ ጉራጌ ቋጣሪ፡፡ ትግሬ ሁሉ ወያኔ፤ ወጣቱ ወመኔ፡፡ አማራው ነፍጠኛ ፤ ደርግ ሁሉ ግፈኛ፡፡ ናቸው እያስባለ ፤ ቁልቁል የሚነዳን ጭ...