Wednesday 30 August 2017

የማንነት ጥያቄ መጥምቁ ዮሀንስ (ዋለልኝ መኮንን ካሳ)


የታሪኩ መግቢያ (ተከታታይ ትረካ ነው)

(በ Derbe Tefera)

‹‹ከለበሱ አይቀር ሱሪ፤
የጥንቱን ነበር የተፈሪ፡፡
ግና አይመችም ለስራ፤
አጣብቆ ይዞኝ በቀኝ ግራ፡፡››
ቅኔው የዋለልኝ ነው፡፡

2007 አመተ ምህረት ነበር ስለ ዋለልኝ መፅሀፍ ላዘጋጅ የተነሳሁት፡፡ ከዛን ጊዜ ጀምሬ ስለ ፓለቲካ ህይወቱ እና እይታዎቹ መረጃዎችን ሳፈላግል ብሎም አስተዳደጉን በተመለከተ የቅርብ ዘመዶቹን እየፈለኩ ቃለ መጠይቅ ሳደርግ ቆየሁ፡፡ ቃለመጠይቅ ካደረኩላቸው ግለሰቦች መካከል የዋለልኝ ዘመድ የሆኑት ዶክተር አየለ ታረቀኝ ይገኙበታል፡፡ ዘግይቸ ከመፅሀፉ ይልቅ አርቲክል ይሻላል የሚል ሀሳብ መጣልኝና ስራየን ቀጠልኩ፡፡ በስተመጨረሻም የምፈልጋቸውን መረጃዎች አግኝቸ ስራየን ወደማጠናቀቁ ተቃረብሁ፡፡

ለመወያየት ያመች ዘንድ ከአርቲክሉ ቀንጨብ እያረኩ ለእናንተም በተከታታይ ክፍል ለማቅረብ ወስኛለሁ፡፡ ከዚህ ቀጥሎ ቅድመ ታሪክ ሀተታውን ለመግቢያ ያክል እነሆ ብያለሁ፡፡
ዋለልኝ እንደ መጥምቁ፦ ያው እንግድህ ዮሀንስ በዮርዳኖስ ወንዝ በሚያጠምቅበት ወቅት ፈጣሪ መጥቶ፡- ‹‹አጥምቀኝ›› ሲለው ዩሀንስ ‹‹እኔ ባንተ መጠመቅ ሲገባኝ እንዴት አንተን አጠምቃለሁ አለው?›› ፈጣሪም ‹‹ሌሎች የኔን ፈለግ ተከትለው ሳይጠራጠሩ እንድጠመቁ እንድሁም ትህትናን ይማሩ ዘንድ እኔን አጥምቀኝ ከዛ ህዝቡ ተከትሎ ይጠመቃል›› ብሎ መለሰለት፡፡ ዩሀንስም በፈጣሪ መጠመቅ ሲችል እርሱ ፈጣሪውን አጠመቀ፡፡ ይህን ተከትሎም ለመጠመቅ ያለው ፍላጎት ጨመረ፡፡ ፈጣሪ ሲጠመቅም ተዓምር ታየ፡፡
.
ዩሀንስ ‹‹እኔ በውሃ አጠምቃችኋለሁ ከእኔ በኋላ የሚመጣው ግን በእሳት ያጠምቃችኋል›› ሲል ተናገሮም ነበር፡፡
አሁን እናንተ እንድትይዙልኝ የምፈልጋቸው ሁለት ነገሮች አሉ፡፡ አንደኛው ሌሎች እንድጠመቁ በምን መልኩ አምነው ተገፋፉ የሚለው ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ከጌታ መጠመቅ በኋላ ምን ተፈጠረ የሚል ነው፡፡

ወደ ማንነት ፖለቲካው አጥማቂ ስንመጣ ብዙ ተከታይ ማፍራቱን ልብ ይሏል፡፡ በወቅቱ የማንነት ጥያቄን ተጨቁነናል ብለው የሚያስቡት ቡድኖች ማንሳት ሲችሉ የማንነት ፖለቲካው አጥማቂም ራሱ በወቅቱ ተጠቃሚ ናቸው ተብለው ከሚታሙት ወገን ቢሆንም ቅሉ ጉዳዩ ይመለከተኛል በማለት ጥያቄውን አንስቶ ለተቀሩት ተከታዮቹ የማንነት ፖለቲካን በማንሳት በውስጣቸው ያለውን ስሜት እንድተነፍሱ በማስቻል ለማንነታቸው ዘብ ይቆሙ ዘንድ በራሱ አንደበትና የሃሳብ ጉልበት ብዕሩን ተጠቅሞ በሩን ከፈተላቸው የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ ይህ አቋም ግን ትክክለኛነቱ መፈተሽ አለበት፡፡ በኢትዮጵያ ታሪክ ጨቋኝ እና ተጨቋኝ አለ ወይ የሚለው ሀሳብ በራሱ አከራካሪ ነው፡፡
ልክ ዮሀንስ ‹‹ከእኔ የበለጠ አጥማቂ ይመጣል›› እንዳለው ፖለቲከኛውም፡- ‹‹እኔ የማንነት ፖለቲካን በማርክሲስት ሌኒኒስት ውሀ አጠምቃችኋለሁ ከእኔ በኋላ የሚመጡት ግን በአብዮታዊ ድሞክራሲ እሳት ይጠምቋችኋል›› ያለም ይመስላል፡፡ (እዚህ ላይ እሳት ስል ዮሀንስ እንዳለው መንፈስ ቅዱስን ማለቴ አይደለም) ፡፡
.
በአስገራሚ ሁኔታ የጌታ መጠመቅን ተከትሎ የዮርዳኖስ ባህር እንደተከፈለው የማንነት ፖለቲካ አጥማቂውም ጉዳዩን ባነሳው ወቅት የአንድነት መንገዱ እንደ ቻይና አስፋልት ተሰንጥቆ የማንነት መስመሮች መሰመራቸው አልቀረም ነበር፡፡ በዚህ የተነሳም ብዙ ውዝግቦች ተፈጠሩ፡፡ ይህ ሁሉ የሆነው በወቅቱ እንደ ታቦ ይቆጠር የነበረውን የብሄረሰቦች ጉዳይ የሚዳስስ ፅሁፍ የያኔው የቀዳማዊ ሐይለ ስላሴ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ልሳን በሆነችው ታገል መፅሄት ላይ ‹‹የብሄረሰቦች ጥያቄ በኢትዮጵያ›› በሚል ርዕስ ታትሞ ለአንባቢ ይፋ መሆኑን ተከትሎ እንደሆነ ብዙዎች ይመሰክራሉ፡፡ ይህ ማለት ግን ፅሁፉ ከመውጣቱ በፊት ማንነትን ያነገቡ እንቅስቃሴዎች አልነበሩም ማለት ሊሆን አይችልም፡፡ የንጉሱን ስርዓት በመቃወም በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ይካሄዱ የነበሩ አመፆችም ማንነትን የተመለተ አንድምታ እንደነበራቸው የሚካድ አይደለም፡፡ ይህ በእንድህ እንዳለ የብሄረሰቦች ጥያቄ ምላሽ ሊሰጥ ይገባዋል የሚል አቋም በይፋ የትግሉ አንዱ አካል መሆኑ ለይቶ የወጣው የፖለቲከኛው መጥምቁን ፅሁፍ ተከትሎ ነው የሚል እምነት በብዙዎች ዘንድ ይስተዋላል፡፡
.
ስለ ዋለልኝ ሲነሳ በአንድ በኩል የነፃነት ፋኖ ወጊ እና አርበኛ ነው የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ ሌሎች ደግሞ ከዚህ የተለየ እሳቤ አላቸው፡፡ ‹‹የበላበትን ወጭት ሰባሪ፤ ለጥላቻ ተወልዶ አገርን በመከፋፈል ያደገና ኢትዮጵያን ከማትወጣበት የፖለቲካ አዘቅት ውስጥ ጨምሮ ያለፈ ብለው ይፈርጁታል፡፡›› የአስገንጣይነት ካባም የተሰጠው ለዋለልኝ ይመስላል፡፡ ዋለልኝ መኮንን እንደ ከፋፋይ፣ አስገንጣይ፣ የጥላቻ ፖለቲካ ቀመር አዘጋጅ፤ ይህም ሳያንሰው የአጥፍቶ መጥፋት የፖለቲካ መንገድ ቀያሽ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ እራሱ አማራ ሆኖ አማራን ነጥሎ እንደ ጨቋኝ አድርጎ ለማቅረብ የሞከረበት አግባብም ከእውነት የራቀ ነው የሚሉ ወቀሳዎች ይሰነዘራሉ፡ የአስገንጣይና ከፋፋይነት ካባው ይስፋው ወይም ይጥበበው ኋላ ላይ የምናየው ይሆናል፡፡ መቼም የልጅ ጃኬት ለአባት፤ የአባት ደግሞ ለልጅ እንደማይሆን ግልፅ ነውና በተመመሳሳይ ለዋለልኝ የተሰፋለት የፖለቲካ ካባ ልክ ሊሆንም ላይሆንም ይችላል የሚል እሳቤ ሊኖር ግድ ነው፡፡ በሶስተኛ ደረጃ የምናገኛቸው ወገኖች በበኩላቸው ስለ ዋለልኝ መኮንን የራሳቸውን ሃሳብ ሰንዝረዋል፡፡ በእነሱ አረዳድ ዋለልኝ ያነሳው ነገር በነውርነት የሚፈረጅ አይደለም፡፡ ሀሳቡም ቅድስናን የተላበሰ ሊሆን ፈፅሞ አይችልም፡፡
ለግንዛቤ ይረዳ ዘንድ በ ታገል (Struggle) መፅሔት ላይ ከታተመችውና ለመጀመሪያ ጊዜ አይነኬ ስለነበረው የብሄር ጥያቄ ዋለልኝ ከከተባት ፅሁፍ ወሳኝ ነጥቦችን በመውሰድ ዘርዘር አድርገን በሚቀጥሉት ቀናት የምንወያይበት ይሆናል፡፡

No comments:

Post a Comment

የፖለቲካ ባህላችን

አየሽ እዚህ አገር ከንቱ ፍረጃ አለ፤ አማኝ ሁሉ አክራሪ፤ ሙስሊሙ አሸባሪ፤ ጉራጌ ቋጣሪ፡፡ ትግሬ ሁሉ ወያኔ፤ ወጣቱ ወመኔ፡፡ አማራው ነፍጠኛ ፤ ደርግ ሁሉ ግፈኛ፡፡ ናቸው እያስባለ ፤ ቁልቁል የሚነዳን ጭ...