Sunday 30 July 2017

አስደንጋጩ የምሁራን ፍርጠጣ (ለ ENN Tv ጋዜጠኛ የተሰጠ ምላሽ)


(መግቢያ ቢጤ) ገዢው ፓርቲ ገና 4 ኪሎ ቤተመንግስት ሲገባ ነበር የፊታችሁ ቀለም አላማረኝም በሚያስመስል አይነት ደካማ አመክንዮ ለምን ጠየቁኝ እኔ የምላቸውን አምነው አይቀበሉም ወይ ታሪክ ለኛ ሊያስተምሩ የሚችሉበት አግባብም የለም በማለት ነበር ምሁራንን ከአንጋፋው የአድስ አበባ ዩኒቨርስቲ ያባረረው፡፡
አድስ የፈጠራ ታሪክ እናስተምራችሁ አዳምጡን ማድመጥ ካልቻላችሁ ግን ብቃት የላችሁም ዩኒቨርስቲውን ለቃችሁ ትወጣላችሁ አይነት የሚመስል ማስፈራሪያ ነበር ነገሩ፡፡ የተባረሩት ምሁራን ቁጥር ወደ 40 ይጠጋል፡፡ አብዛኞቹ ወደ ውጭ አገር ኮበለሉ፡፡ ኮብልለውም በግለሰብ ደረጃ ተጠቀሙ እንጅ አልተጎዱም፡፡ አገሪቱ ግን አንጋፋ ምሁራኖቿን ነበር በወቅቱ ያጣችው፡፡

The Ethiopian Herald የተሰኘው ጋዜጣ "Ethiopia's face of brain drain: Leaving while productive, returning as retirees" በሚል ንዑስ አርዕስት ስለ ምሁራን ስደት ሰሞኑን መዘገቡ ይታወቃል፡፡ ENN ቴሌቪዥንም በዚሁ ጉዳይ ላይ ዳጉ በተሰኘ ፕሮግራሙ (ሄራልድን አጣቅሶ) ሽፋን ሰጥቶ ነበር፡፡ ነገር ግን ከተወያዮቹ መካከል አንደኛው ጋዜጠኛ የችግሩ መንስኤ "ኢኮኖሚያዊ ነው" ብሎ የደረሰበት ድምዳሜ ህፀፅ አዘል ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡ ምክንያቱም ለአብነት ያክል 40ዎቹን የእውቀት አዝመራ ባለቤቶች ጭምር ያሰደደው ድህነት አይደለም፡፡ ስንቱ ምሁራን ናቸው አገራቸውን ማገልገል እየፈለጉ መንግስት እግራቸውን የቆረጣቸው፡፡ የአካዳሚክ ነፃነት በሌለበት አገር እንኳን የወጡት ሊመለሱ አገር ውስጥ ያለውም መውጫ ቀዳዳ ፈላጊ ነው፡፡ ይህ የሆነው ደግሞ ደምወዝ ስላነሰ ብቻ ሳይሆን የመንግስት ጉንተላ አላስቀምጥ ስላላቸው ነው፡፡
 ለምሳሌ ያክል የአድስ አበባ ዩኒቨርስቲ ድምቀት የሆኑትን ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋና ዶ/ር መረራ ጉድናን ማንሳት ይቻላል፡፡ አንቱ የተባሉት እነዚህ ሁለት የእውቀት አባቶች በገዥዎች የተነሳ ዋጋ እየከፈሉ ነው፡፡ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ ከሚወደው የመምህርነት ሙያ ተመንጭቆ 6 ኪሎን ለቀህ ውጣ ሲባል ዶ/ር መረራ ደግሞ ከርቸሌ ሆኗል እጣው፡፡ ሁለቱ ምሁራን ሚዛናዊ በሆነ ትችት ነው የሚታወቁት ነገር ግን እኛ ብቻ ነን አዋቂ ማጨብጨብ እንጅ ወደኛ ትችት መሰንዘር ወንጀል ነው ተብለው የግፍ ሰለባ ሆኑ፡፡ ስለዚህ እውነት ጋዜጠኛው ከልቡ ነው የተናገረው ወይስ መንግስትን ላለማስቀየም ነው? ብለን መጠየቁ ትክክል ነው ባይ ነኝ፡፡ እንዲህ አይነት ትንታኔ ከጋዜጠኝነት ስነምግባር ያፈነገጠ ወገንተኝነት ነው፡፡
በአገር ፍቅር ስሜት የነደዱ ስንት ምሁራን በአለም አቀፍ ደረጃ እንደ ጨው ተበትነው ቀርተዋል፡፡ አንዳንዶችማ በየ ሚድያዎች ምኞታችን አገራችንን ማገልገል ነው ሲሉ ሆድ ያስብሳሉ፡፡ ይህ ምኞታቸው እንኳን ደህና መጣችሁ ብሎ የሚቀበል መንግስት ባለመኖሩ ምክንያት እንደጉም ተነነ፡፡ ለአገር አሳቢ መንግስት ቢኖረን ኖሮ "ቀይ ምንጣፍ አንጥፎ በፓሊስ ኦርኬስትራ የታጀበ አቀባበል" ይደረግላቸው ነበር፡፡

የምሁራን ፍርጠጣ እልባት ካልተሰጠው ዩኒቨርስቲዎቻችን እንደ ንብ አልባ ቀፎ ባዶ መቅረታቸው ግልፅ ነው፡፡

ንቡ ሄደ ኧረ ንቡ ሄ፤
አገጣውን ጥሎ ፤
ከአንዱ አገር አንዱ አገር፤
ይሻለኛል ብሎ፡፡

...ሲል ንቡ የሄደበት የአማራ ገበሬ እና አናቢ እንዳንጎራጎረው ዩኒቨርስቲዎችም የምርምርና እውቀት አገጣቸው ብቻ እንዳይቀር ያስፈራል፡፡

ማንም ተጨቁኖ መኖር አይፈልግም፡፡ የተሻለ ደመወዝ ባይሰጣቸው እንኳ ተፈጥሯዊ ፀጋ የሆነውን ነፃነት ሊነፈጉ አይገባም፡፡  ስለዚህ ለምሁራን ፍርጠጣ ዋናው ችግር ኢኮኖሚያዊ ብቻ ሳይሆን ፓለቲካዊም ጭምር ነው፡፡ ዋናው እና አነሳሽ ምክንያቱ (Major and triggering cause) ኢኮኖሚያዊ ነው ማለት የደከመ አመክንዮ ነው፡፡ ፍረጃ (Hasty Generalization) አይነት ህፀፅ ስለሆነ ሊታረም ይገባል፡፡ M. Twain "It is easier to fool people than to convince them that they have been fooled" እንዳለው ቢሆንም ቅሉ ህዝቤ መቸም ሁሌ አይሞኝም፡፡

በማስረጊያነት እውነት ሁሌም ያሸንፋል የምትለዋን ያዙልኝ፡፡


የምሁራን ስደት በእስካሁኑ ይብቃ!

(ደርብ ተፈራ)

የወልቂጤ ዩኒቨርስቲ ባልደረባ እና የፓለቲካል ሳይንስ ምሩቅ)

Saturday 29 July 2017

ስልጣን እና ሀብት በዘመነ ኢህአዴግ

In Ethiopia, Power is a short cut to get rich.

እውነታው ይህ ነው! ኢትዮጵያ ውስጥ የመንግስት ስልጣን ህዝብን ማገልገያ ሳይሆን ሀብት ቁንጮ ላይ ለመድረስ አቋራጭ ነው፡፡ ራስ ወዳድነት የባለስልጣኖቻችን መገለጫ ሆኗል፡፡ እስኪ ማነው "እኔ የአገር ሀብት አልነካሁም ንፁህ ነኝ የሚል ፃድቅ ባለስልጣን?" ሁሉም በሚባል ደረጃ በሙስና ተጨማልቀዋል፡፡ ገለልተኛ የሆነ አካል ጉዳዩን ቢያጣራው የሁሉም ጉድ ይወጣ ነበር፡፡ ታድያ ምን ዋጋ አለው!  ፀረ ሙስና ኮሚሽን ሳይቀር ተጠሪነቱ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ነው፡፡ ኮሚሽኑ እከሌ ላይ ምርመራ ይጀመር የሚል ትዕዛዝ ከምኒልክ ቤተመንግስት ካልመጣለት ዘረፋ ሲካሄድ እያየ ጆሮ ዳባ ልበስ ነው የሚለው፡፡
የኛ ባለስልጣኖች ሆዳም ስለሆኑ የአገሪቱን ሀብት ብቻ በልተው አይጠግቡም፡፡ ዜጎችንም ከምድሯ ያጠፋሉ አሁንም እያደረጉት ያለው ነገር ይህ ነው፡፡

በተደጋጋሚ በፌስቡክ ገፄ ላይ ስላችሁ እንደነበረው በአገራችን ኢትዮጵያ ሙስና ተዘርቶ የሚበቅልበት ለም የሆነ የማህበረሰብ ባህል አለ፡፡
ሲሾም ያልበላ፤
ሲሻር ይቆጨዋል፡፡
ይህ አባባል የማንም አይደለም የኛው ነው፡፡ ባለስልጣናት ያገኙትን ወርቃማ አጋጣሚ ተጠቅመው የአገር ሃብትና ንብረትን ቢዘርፉ ችግሩ የእነሱ ብቻ ሳይሆን ያሳደጋቸው ማህበረሰብም ጭምር ነው፡፡ መንግስታዊ ሌቦችን የወለደው ማህበረሰብ ስርቆቱ ለሚያስከትለው ምጣኔ ሐብታዊ እና ሌሎች አገራዊ ቀውሶች ተጠያቂ ነው፡፡ እንደኛ ማህበረሰብ አንተ ተሿሚ ከሆንክ ወንበሯ ላይ እስካለህ ድረስ ጠንክረህ መዝረፍ አለብህ፡፡ ይህ ካልሆነ ወንበሩን ያጣኸው ቀን ይቆጭሀል፡፡ ሙስና እና ብልሹ አሰራር ተዘርቶ ቡቃያው የለመለመበት ምቹ የማህበረሰብ ባህል የት ነው ያለው ብሎ ለሚጠይቅ አድራሻው ኢትዮጵያ ውስጥ ነው ቢባል መሳሳት አይሆንም፡፡ የኛ ማህበረሰብ ‹‹የአባትህ ቤት ሲዘረፍ አብረህ ዝረፍ›› እያለ ዝርፊያን ያበረታታል፡፡ ለዘራፊዎችም ድጋፉን ይሰጣል፡፡ አብረህም እንድትዘርፍ ነፃነት ይሰጥሀል፡፡ ከዛ ልማታዊ ሌባ የሚል ታፔላ ይለጠፍብሀል፡፡
     ሁሉም በየፊናው  የአገር ሃብትን ከመዘበረ አገራዊ የገንዘብ ካዝናችን ባዶ መሆኑ ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ ኬንያውያን ‹‹አሁን ተራው የእኛ ነው›› የሚሉት አባባል ነበራቸው፡፡ አንድ ጎሳ ስልጣን ላይ ከወጣ የድርሻውን አንስቶ ይወርዳል፡፡ በእነሱ ባህል ስልጣን እጅህ ውስጥ ከገባ ዘረፋው ያንተ ተራ ነውና የድርሻህን ማንሳት አለብህ፡፡ ሩቅ ሳንሄድ እኛም አገር እየሆነ ያለው ነገር ከዚህ የተለየ አይደለም፡፡
     ሙስናን መዋጋት መጥፎ ባህልን ከማስወገድ መጀመር አለበት ብየ አምናለሁ፡፡ የሰው ልጅ ያደገበትን አካባቢ ይመስላል፡፡ የምንኖርበት ማህበረሰብ የስብዕናችንን መሰረተ ድንጋይ ያስቀምጣል፡፡ መጥፎ ማህበረሰብ ተዓምራዊ በሆነ ሁኔታ ካልሆነ በስተቀር ምሉዕ ስብዕና ያላቸውን ግለሰቦችን ለአገር አያበረክትም፡፡ ‹‹ከአህያ ጋር የዋለች ጊደር…›› እንድሉ በክፉ መንጋ መሀል ያሉ ጥቂት ግብረገብ ግለሰቦችም መልካምነታቸው ሲበከል አይቆይም፡፡ ስለዚህ ለሙስና አወንታዊ አመለካከት ባለው ማህበረሰብ ውስጥ ፈፅሞ ሙስናን መዋጋትና ድል ማድረግ አይቻልም፡፡ ብልሹ አሰራርን ለመዋጋት ብልሹ ባህልን ማስወገድ ወሳኝ ቅድመ ሁኔታ የሚሆነውም ለዚህ ነው፡፡ ስለዚህ ‹‹ሙስናን መዋጋት ባህልን ከማደስ ይጀምራል፡፡›› ሙስናን በነውርነት የሚፈርጅ ባህል ስንገነባ ያኔ ከሙስና የፀዳ አሰራር ሰፍኖ እናያለን፡፡
     ሙስና በሁሉም ሃይማኖቶች የተወገዘ እኩይ ተግባር ነው፡፡ ለአብነት ያክል ከሙሴ ህግ ጀምሮ ሙስና የተከለከለ መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ ከክርስትና እስከ እስልምና ሃይማኖት ያሉ አስተምህሮቶችን ብናይ ሙስና ሃጢያትና ሀራም መሆኑን እንገነዘባለን፡፡ መንፈሳዊነት ቦታውን ለቁሳዊነት ሲለቅ የሙስና ዛፍ ያንሰራፋል፡፡ የሰው ልጅ አዕምሮና አስተሳሰብ እንዳይዝግ የሚከላከለው ሰውኛ ሞራሊቲም ላይመለስ ይኮበልላል፡፡
     ሙስናን ህጋዊ ማዕቀፎችን በማዘጋጀት ብቻ ልንከላከለው አንችልም፡፡ ፀረ-ሙስና ኮሚሽንም ብቻውን ለውጥ አያመጣም፡፡ በመንግስት መስሪያ ቤቶች፣ የልማት ድርጅቶች እና የግል ድርጅቶች ደረጃ ቀርቶ በግለሰብ ደረጃ የግለሰቦች የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ቢቋቋም ከንቱ ልፋት ነው፡፡ ሙስናን ለመከላከል ዋነኛ መሳሪያው የግለሰቦች አስተሳሰብ ላይ መስራትና ሙስናን የሚፀየፍ ባህል መፍጠር ነው፡፡
     ሙስናና ብልሹ አሰራር ከአዕምሮ ዝገት የሚመነጭ ማህበረሰባዊ በሽታ ስለሆነ የዝገት መከላከያው ደግሞ ግብረገብ የሆነ ትውልድ መፍጠር ብቻ ነው፡፡ ገንዘብ አምላኪ ትውልድ ባለበት አገር ህሊና ዳኝነቱን ለሆድ ይለቃል፡፡ መጨረሻውም ተባብሮ አገርን መዝረፍና የራስን ጥቅም ማሯሯጥ ነው፡፡ ለብሄራዊ ጥቅም ሳይሆን ለግል ጥቅም ማሰብ የአስተሳሰቦች ሁሉ የበላይ ይሆናል፡፡ ‹‹ሰርቶና ለፍቶ ማግኘት›› ሳይሆን ‹‹አጭበርብሮ ሃብትን ማጋበስ›› እንደ ጀግንነት ይቆጠራል፡፡ ጉዳይ ለማስፈፀም ‹‹በእግር ሳይሆን በእጅ መጓዝ›› አማራጭ የሌለው አማራጭ ሆኖ ይመጣል፡፡ ያኔ ‹‹ምን ታውቃለህ ሳይሆን ማንን ታውቃለህ እና ምን ይዘህ መጣህ›› ትባላለህ፡፡
    ከዕለታት አንድ ቀን መሬት አልባ የሆነ ወጣት አርሶ አደር የመሬት ኮሚቴዎችን ስንዝር የምታክል መሬት እንኳን ስጡኝ ብሎ ይጠይቃቸውና እነሱም ለውለታቸው ጉቦ መክፈል እንዳለበት ይነግሩታል፡፡ ስለ ጉቦ ሲነሳ በሁኔታው የተናደደው ወጣት ያንጎራጎራት ዜማ ትዝ አለችኝ፡፡
በሬውን አረዱት አርሶ ´ሚያበላውን፤
ላሚቱን አረዷት ጥጃ ´ምትወልደውን፤
ማረድስ ኮሚቴን ጉቦ ´ሚበላውን፡፡
     በጣም የሚያሳዝነው ነገር የአገር ሀብት በሙሰኞች ሲመዘበር ‹‹አይተን እንዳላየ›› የምናልፈው ብዙዎች መሆናችን ነው፡፡ ማህበረሰባችን ‹‹ዝምታ ወርቅ ነው›› ይልሀል፡፡ እኔ ግን እልሀለሁ ‹‹ወርቁ ከብሄራዊ ባንክ ሲዘረፍ›› እያየህ ዝም ብትል ዝምታህ እንኳን ወርቅ ሊሆን የነሀስ ዋጋም አያወጣልህ፡፡
     ሙስና የአገር እድገት ነቀርሳ ነው፣ መልካም መስተዳደርን ያዳክማል፣ የኢኮኖሚ አቅምን ያዳሽቃል፣ ፍትህን ያዛባል፣ የእኩልነት ሚዛንን ያበላሻል፣ ሰብዓዊ ክብርን ይንዳል፣ ህዝብን ጦም ሊያሳድርም ይችላል፡፡ በአጠቃላይ ሙስና ሰደድ እሳት ነው አገርን ያቃጥላል፡፡ ስለዚህ መንግስታዊ (ልማታዊ) ሌቦችን ወልዶ ማሳደግ መቅረት አለበት፡፡
ሲሾም የበላ አፈር ይብላ፡፡ ‹‹ውጉዝ ከወ አርዮስ ፡፡››


ደርብ ተፈራ
(የወልቂጤ ዩኒቨርስቲ ባልደረባ እና የፓለቲካል ሳይንስ ምሩቅ)

የፖለቲካ ባህላችን

አየሽ እዚህ አገር ከንቱ ፍረጃ አለ፤ አማኝ ሁሉ አክራሪ፤ ሙስሊሙ አሸባሪ፤ ጉራጌ ቋጣሪ፡፡ ትግሬ ሁሉ ወያኔ፤ ወጣቱ ወመኔ፡፡ አማራው ነፍጠኛ ፤ ደርግ ሁሉ ግፈኛ፡፡ ናቸው እያስባለ ፤ ቁልቁል የሚነዳን ጭ...